ጭለማና ብርሃን

You might also like

Download as pdf or txt
Download as pdf or txt
You are on page 1of 9

 

ጭለማና ብርሀን
ለስብሀት ገብረእግዚአብሄር

(አጭር ልቦለድ - ሉሉ ከበደ)

የመሬታችን ወዘናው እስከመጨረሻዋ ጠብታ ተሟጧል። እንኳን አዝርእት የራሱም ሳርና ቅጠል
በላዩ ላይ አልበቅል ብሎ፤ የሚበቅለውም ጫጭቶና መንምኖ ፍሬ አልሰጥ በማለቱ መሬቱ አሸዋና
ድንጋይ ብቻ ከሆነ ቆይቷል። ጎርፍና ንፋስ የቻለውን ያህል በየጊዜው ተሸክሞ እየሄደ አገሩን
ምድረበዳ አድርጎታል። በየማሳውም የተዘራው እህል አገር ከሚያክል ሁዳድ አራትና አምስት ቁና
እየተመረተ፤ ቢዘንብም ባይዘንብም እርሀብ የህይወታችን የሰውነታችን አካል ከሆነ ቆይቷል።
በቀየው ለወጉ ከብቶች ይሰማራሉ። በሸሆናቸው ድንጋይን ከድንጋይ ሲያጋጩ ሲያንኳኩ ውለው፤
አንጀታቸው እንደተጣበቀ ወደ በረት መመለስ የለት ተለት ህይወት ትእይንት ከሆነ ከርሟል።
ሁሉም ከአጥንትና ቀንድ ብቻ የተፈጠሩ ይመስሉ ነበር። ከብቶች። ምሽት ላይ የመንገዱን አቧራ
እንደጉም እያናኙ ወደመንደር ይነዳሉ።

እናቴን ዛሬ ብታይዋት ጉስቁልና ያን መካከለኛ ሰውነቷን ገንዞት፤ መንምናና ታርዛ፤ ቀይ ገጿ


ወይቦ፤ የጉንጮቿ አጥንቶች ፈጠውና አይኖቿ ጎርጉደው ትታያለች። ከጋረዳት ደመና በስተጀርባ
የብርሀኗ ድምቀት ወለል ብሎ እንደሚታይ የማለዳ ፀሀይ፤ የናቴም ውበቷ መላሰውነቷን ከወረረው
ከዚያ ሁሉ ጉስቁልና በስተጀርባ፤ ከሁለመናዋ ይነበብ ነበር። ፈገግ ስትል የጥርሶቿ ውበትና
ንጣት፤ የሚያስገርም ነገር አጋጥሟት አይኖቿ ሲፈጡ ድምቀታቸውና ውበታቸው ህያው ነበር።
ቢደላት ኖር ባገር አለች የተባለችን ቆንጆ የምታስከነዳ እናት ነበረች። የኔ እናት… አርሶ አደሯ።

አባቴም ቢሆን እርሻ ላይ ወይፈን እገራ ብሎ፤ ከወይፈኑ ጋር “ቀንበር ትገባለህ አልገባም”
ሲታገሉ፤ ወይፈኑ ማጅራቱ ላይ የተጫነውን ቀንበር ሊጥል ሽቅብ ሽቅብ አናቱን እየወረወረ
ሲመናጨቅ፤ በቀንዱ ያባቴን አፍ አግኝቶት ኖሮ፤ ከላይኛው የፊት ጥርሶቹ አንዲቷን አወለቀ።
ረዘም ያለና አንደንስር አሞራ ምንቃር መሀል ላይ ጎበጥ ያለው አፍንጫው እስከላይኛው ከንፈሩ
ወረድ ያለ ነው። አባቴ ፈገግ ሲል ደስ ማለቱ የጥርሱ ውልቃት ፍንጭት አንጂ አደጋ እንኳ
አይመስልም ነበር። ፊቱ ክብና አጠር ያለ ነው። እስከመሀል አናቱ የዘለቀ በራው ጠይም ፊቱን
ረጂም አስመስሎታል። የተንዠረገገ ሪዙ አንገቱን ሸፍኖታል። አይላጭም። በጣቱ ማፍተልተል
ይወዳል።

እኔ በተወለድኩበት ዓመት ዝናብ ጠፍቶ በየማሳው የነበረ ሰብል በቡቃያው ስለቀረ ረሀብ አገሩን
ወሮት ነበርና እናቴ “በእድሉ ያድጋል ብላ” ስሜን “በድሉ” አለችን አሉ። ሶስተኛ ልጅ ነበርኩ።
አንጋፋ ወንድማችን ዘመድኩን አስራሁለት ዓመቱ ነበር። ተከታዩ ባዩሽ ዘጠነኛዋን ይዛለች። እኔ
ሰባተኛዬን ይዤ ነበር። የኔ ተከታይ አምስተኛዋን፤ የታናሼታናሽ ሶስተኛዋን፤ የታናሼ ታናሽ
ታናሽ አንደኛውን ይዟል። ስድስት አናት ባስራአምስት ዓመት ራስ በራስ ላይ ተወልደን፡
ተኮልኩለን፤ ሁላችንም እንዋደድ ነበር። ሁላችንም አለን።

አባታችን ባንድ ጥማድ በሮች ጫንቃ ላይ የጫነውን ቀንበር ሲያጠብቅ ሲያላላ፤ እርፍ ሲያሳጥር
ሲያዝረዝም እየዋለ፤ ካባቱ ከወረሳት አራት ጥማድ መሬት ላይ በምናገኛት ሰብል ነበር ውለን
የምንገባው።
 
Page 1 of 9 
 
 

የአርሶ አደር ኑሮአችን ግራ ቀኝ የማያላውስ፤ እናትና አባቴ ከተጋቡ ያለፉትን አስራአምስት


ዓመታት እንደነገሩኝ እናም እኔም በእድሜዬ እስከማውቀው ድረስ፤ ኑሮ ውሀ ልኩን ጠብቆ መሬት
ለመሬት ኩልልል እያለ ሲወርድ የማስተውለው ነበር። ይሁንና ቤተሰባችን ፍጹም ደስተኛና ጤናማ
ነበርን።

አባቴ ማታ ከእርሻ ደክሞት ሲገባ እናቴ በዚያ የማይጠገብ ጎስቋላ ፈገግታዋ ተቀብላ እግሩን፤
እጁን፤ እንዲታጠብ ውሀ ለብ አድርጋ ካቀረበችለት በሗላ፤ ቀድማ እኛን አብልታ ላባቻችን
የድርሻውን ከማጀት ያስቀመጠችለትን እራት አሙቃ ታቀርብለታለች። መጀመሪያ ለሷ ያጎርሳል።
ከዚያ ለሁላችንም ሁለት ሁለቴ፤ ከዚያ የተረፈችውን በላልቶ ያችን የሚወዳትን ቀጭን የገብስ ጠላ
በሽክና ከናቴ ተቀብሎ ወደ መደብ ይወጣል።

‘’ ነይ እስቲ አትጠገብ፤ አረፍ በይ እናውጋ። አንቺም ከነዚህ ልጆችና ፍየሎች ጋር ላይ ታች


ስትይ ከኔ ይብሱን ደክመሽ ነው የምትውይ፤ ልጆቼም ወዲህ ወደ መደቡ ኑ የማወጋችሁ አለኝ”
ይለንና ሁላችንም በአባታችን ዙሪያ እንሰበሰባለን። የሳር ቤት ጎጆአችን ትደምቃለች። ከምሶሶው
ስር መቅረዝ ተሰርቶላት ጭልጭል የምትለው ኩራዝ ባባታችን ዙሪያ ስንሰበሰብ የማሾ ያክል
ደምቃ ትታየናለች። ጥቁር ጢሷ በቀጭኑ ወደጣራ ቀጥ ብሎ ይወጣና እላይ ሲደርስ አንደጃንጥላ
ብትን ይላል።

አንዷን ሽክና ጠላ ከጨረሰ በሗላ እናቴ ሁለተኛውን ስትደግመው ፉት እያለ ጨዋታውን


ይጀምራል።

“የአምናው ክረምት አለቅጥ ሰምሮ ነበር። ቡቃያው ሁሉ አምሮ ነበር። ምን ያደርጋል አባቴ
ከአባቱ የወረሰው መሬት እኔ ላይ ሲደርስ ታከተው መሰለኝ ከድካም በቀር ፍሬ አልሰጥ ብሏል።
አምና ያዘመርነው ዘንድሮ ለዘር እንኳ አልተረፈም፤ አይደል አትጠገብ?” አለና ወደ እናቴ
ተመለከተ።

በቅሬታ ፈገግታ ባዎንታ ራሷን ነቅንቃ መለሰችለት።

“ አዎ ምንም የለም “ አለና ፊቱን ወደኛ መልሶ “ በጋው አለቀ። ልጆቼ መሬታችን ነጥፏል።
ክረምት መግባቱ ነው። ያለ እረፍት አርባ ዓመታት ታረሰ። መሬትም እንደሰው ካልመገቧት
አትሰራም። ፍሬ አትሰጥም። ፍግ የለም። ማዳበሪያ የለም። በሮቼም እኔም አይደክሙ ደክመን
የምናዘምረው ከቁና አልፎ ድብኝትም አልሞላ ብሏል። የዘንድውን ክረምት ልጆቼ ልትራቡ ነው።
ያ ከመሆኑ በፊት ግን አጎቴ አብየ ከልካይ መሬት እሰጥሀለሁ ብለውኛል። ጫካ መንጥረህ አልማ
ብለውኛል። ደጋ ወጥቼ ሁለትም ሆነ ሶስት ጥማድ መሬት እመነጥራለሁ። ዘንድሮ ለም መሬት
አርሼ ለከርሞ ወፍራም አንጀራ እንበላለን ልጆቼ፤ የዘንድሮውን ክረምት ግን የናታችሁ መሶብ ወና
መክረሙ ነው። አንጀታችሁም መራቡ።” አለና በፍቅር አይን እየተመለከተን በቅሬታ ፈገግ አለ።
ረጂም ሪዙን በጣቱ አፍተለተለ።

እናታችንም አራሴን እየደባበሰች “ እሱ አንድዬ ያውቃል። የከፈታትን ጉሮሮ እንዴት


እንደሚዘጋት፤ አትጨነቅ አካሌዋ። ቀድሞውንም ከእግዚአብሄር ጋር እንጂ ልጆቻችንን ለብቻችን
አላሳደግናቸውም። የወደፊቱንም እርሱ ያውቃል። ነፍስህን አታስጨንቃት። የሚሆን ይሆናል።”
አለችና ሶስተኛውን ሽክና ጠላ ልትሞላለት ወደ ማጀት አቀናች።

 
Page 2 of 9 
 
 

“ ልጆቼማ ቶሎ ቶሎ እንዲያድጉ ወፍራም ዳቦ ያስፈልጋቸዋል። አሁን የተነገወዲያው ሰንበት


አጎቴ ዘንድ ደጋ ወጥቼ የሚሰጠኝን መሬት አየዋለሁ። በልግ መጣሉ ስለሆነ የሚመነጠርም ከሆነ
መንጥሬ ገምሼ አሰናዳዋለሁ።”

ይህንን ባለ በሶስተኛው ቀን ነበር አባቴ ተነስቶ ደጋ የወጣው። እንደደረሰም፤ የናቱ ወንድም አጎቱ
አብየ ከልካይ ካንድ መለስተኛ ተራራ ግርጌ ወደሚገኝ ለም መሬት ይዘውት ሄዱ። በለምለም
እጽዋትና በረጃጅም ሳር የተሸፈነው ረግረጋማ መሬት በርቀት ከሚታየው የተራራ ሰንሰለት ድረስ
ፍጹም አረንጓዴ ምድር ነበር።

አብየ ከልካይ ትንሽ ጉብ ያለ ቦታ ላይ ቆሙና በዘንጋቸው አሻግረው እያመለከቱ፤


“ ያውልህ፤ ከዚ የጀመርክ እስከዚያ ድረስ፤ ከዚያ በመለስ ጉልበትህ እቻለ ድረስ፤ መንጥረህ
እረስ። ልጆችህ እንዳይርባቸው በርትተህ እረስ። እኔ እንግዲህ ቀኔም ደርሷል፡ እንዲያው አንድ
ነገር ሳላቆናጥጥህ እንዳልሞት ብየ ነው። እህል አይቶ የማያውቅ ድንግል መሬት ነው።” አሉና
የተባዘተ ጥጥ የመሰለ ሪዛቸውን ቁል ቁል እየሳቡ ላፍታ ዝም አሉ።

አባታችን አላመነታም። ከቆሙበት ቦታ ካለችው ስብሳብ ጀምሮ ምንጠራውን ተያያዘው። በቁጥቋጦ


በወይራና በክትክታ ዛፎች የተጨናነቀው መሬት አንዲት ጥማድ ለመመንጠር ሁለት ሳምንት ነበር
የፈጀበት። ጅብ፤ ቀበሮ፤ ጥንቸል፤ ዘንዶው እባቡ ሁሉ ተደላድለው ይኖሩበት የነበረ አስፈሪ ጫካ
መሆኑ አባቴን ሳያሳስበው አልቀረም። ከሁም የከፋው ግን አካባቢውን የነገሰበት የዝንጀሮና የዱር
አሳማ መንጋ ለአዝርእት ጸር መሆኑ ነበር። ከሁለት ሳምንት በሗላ ወደቤት መጣ። መሬት
አይደለም ዳቦ ያገኘ ያክል ነበር ደስ ብሎት ያበሰረን። ይብሱን ሰውነቱ መንምኖ ነበር
የተመለሰው።

ብዙም ውሎ አላደረ በሁለተኛው ቀን በሮቹን ይዞ ደጋ ወጣ። አዲሱን መሬት ገምሶ፤ አለስልሶ፤


ለዘር አዘጋጅቶ፤ወደቤት ተመለሰ። እንደገና ካንድ ቀን እረፍት በሗላ ሁለተኛውን ጥማድ መሬት
ሊመነጥር ተሰናብቶን ሊወጣ ሲል፤ ካልተከተልኩ ብየ አስቸገርኩ። እናቴ የአብየ ከልካይንም እዚያ
መኖር ግምት ውስጥ ከታ ነው መሰለኝ “ምንም አይሆን ይከተልህ” አለችውና አባቴ ትከሻ ላይ
ተጭኘ ወደሚመነጠረው ጫካ ወደ አዲሱ መሬታችን የእግር ጉዞ ተጀመረ።

ማለዳ የተነሳን ዐሀይ ከአናት በላይ ከዋለች በሗላ አዲሱ መሬታችን ደረስን። ከሰዓቱን አባቴ
የለመደውን ምንጠራ ተያያዘው። ዛፎቹን ሲቆርጥ፤ ሲነቅል፤ ሲገነጥል፤ ፍጥነቱና ቅልጥፍናው
እያስገረመኝ ላፍታ ቆም አልኩና ካየሁት በሗላ እኔም ወደስራዬ ሄድኩ። ከርሱ ስርስር
እየተከተልኩ፤ ትንንሽ ቅርንጫፎችን እየሰበሰብኩ፤ ጎጆ ቤቶችን እየሰራሁ ጨዋታ ቀጠልኩ።
ነፍሳትና ቢራቢሮ ሳይ እየተከተልኩ፤ እያሳደድኩ፤ አንዷን ስይዝ አንዷን ስለቅ እናም አባቴ
መኖሪያቸውን ሲያተረማምሰው ከየስብሳቡ ውስጥ ቱር እያሉ የሚያመልጡ እናትና ልጅ
ጥንቸሎችን እያየሁ ስደነግጥ፤ አንዳንዴም ስደነቅ፡ ሂደቱ ቀጠለ። የሚኖሩበት ዛፍ ከስር
በመጥረቢያ ሲናጋ፤ ጎጆአቸው ሲፈርስ፤ እንቁላላቸው ሲረግፍ፤ የፈለፈሉአቸው ጫጩቶች ሲበተኑ፤
እናትና አባት ወፎች ይመስሉኛል፤ ተናደው፤ ተቆጥተው፤ በንዴትና በሀይል ይመስለኛል ለኔ፤ ወደ
ሰማየሰማያት ብርርርር… ይላሉ። በቀጥታ ሽቅብ። ካይኔ አስኪሰወሩ አንጋጥቼ እመለከታቸው
ነበር። እኔም እንዳንጋጠጥኩ አነሱም ሽቅብ ተናደው አንደከነፉ እልልል…ም ብለው ደመናው
ውስጥ ገብተው ከአይኔ ይሰወራሉ። እኔም ወደ አባቴና ወደ ምንጠራው እመለሳለሁ።

 
Page 3 of 9 
 
 

በዚያ የልጅነት አእምሮዬ ቤታቸው ሲናድ መድረሻ ፍለጋ የሚሯሯጡት ፍጥረታት መጨረሻቸው
ምን እንደሚሆን ለማወቅ ያስጨንቀኝ ነበር።

“አባባ ለምንድነው ጥንቸሎቹን የምታስሮጣቸው?” አባቴን እጠይቃለሁ።

እኛን ለመመገብ ሲል የተፈጥሮ ቤታቸውን እንደሚያፈርስባቸው ይነግረኛል።

“በቃ ቤታቸውን ተውላቸውና ወደቤታችን እንሂድ”

ሳቅ ብሎ በፍቅር ይመለከተኝና “አየህ የኔ ልጅ… ይህ የምታየው ጫካ ሁሉ ለነሱ ቤት መሆን


ይችላል። ከዚህ ሄደው እዚያ መግባት ይችላሉ። ቤት ያበጃሉ። ይኖራሉ።’’

“ከዚያ ሲያፈርሱባቸው የት ይሄዳሉ?”

“ከዚያ ሲያፈርሱባቸው ደሞ ሌላ ቦታ ይሄዳሉ”

“ሌላ ቦታ ሲያፈርሱባቸውስ?”

“ደሞ ሌላ ቦታ” ይለኛል እየሳቀ።

አልገባኝም። ከሁሉም አቅጣጫ ፍጥረታት መኖሪያ ቀያቸው ሲፈርስ ሲናጋ የመጨረሻ መሄጃቸው
የት አገር እንደሆነ።

አንዲት ነጭ ቢራቢሮ ስትውለበለብ ድንገት አየሁና እሷን ላሳድድ ሄድኩ። ነገር ግን ወዲያው
ንፋስ ይዟት ካጠገቤ ጥርግ አለ። ወዲያውም አንዲት ቢጫ ወፍ ከፊቴ ቱር አለች። ከታች
በመጥረቢያ የነበረችበትን ግንድ አባቴ ሲቆርጠው ቀጥ ብላ ወደ ሰማየሰማያት ከነፈች። ሽቅብ
እየከነፈች አየር ላይ ቆም አያለች፤ ሽቅብ እየከነፈች ቆም እያለች ወደላይ ወጣች ። አንጋጥቼ
መድረሻዋ የት እንደሚሆን እስከጠፈሩ ተከተልኳት። ወጣች ወጣችና ካይኔ ተሰወረች። ከደመና
ውስጥ ፈለኳት። የለችም።

ድንገት ነበር አባቴ የሲቃ ጩኸት ሲያሰማ መብረቅ የጮኸብኝ ያክል ደንግጬ ዘወር ያልኩት።
አንዲት ትልቅ ውሻ የምታክል ፍጥረት አፏን አስከመጨረሻ ከፍታ እግሩን፤ ባቱን፤ በሙሉ ጎርሳ፤
የነከሰችውን ሙዳ መንጭቃ ለማምለጥ ይመስላል እያናፈረች ልትነጭ ስትታገል አባቴም “ኡኡ”
እያለ ሊያስለቅቃት በያዘው የእንጨት ግንጣይ ሲደበድባት እኔ ወደምደርስበት ጠፋኝ። መላ
ሰውነቴ፤ የልጅነት አካላቴ እየተንቀጠቀጠ፤ እየተንዘረዘረ ስጮህ፤ አባቴም ሲጮህ፤ አውሬዋም
ስታናፍር፤ ስትጮህ፤ ምድር ተከፍታ አትውጠኝ፤ ሰማይ ተከፍቶ አይውጠኝ፤ “አባባ! አባባ!”
እያልኩ በሲቃ ለራሱም ፈተና ላይ ወደወደቀው አባቴ እቅፍ የነፍስ ይዞኝ ብርርር እያልኩ ሮጥኩ።
አባቴና አውሬዋ የሞት የሽረት ትግል ይዘዋል። ከእግሩ ደም ይንፏፏል። ከዱላ ብዛትም ይሁን
ወይም አውሬዋ የምትፈልገውን ስላገኘች ብቻ ለኔ ሊገባኝ በማይችል ሁኔታ ድንገት አባቴን
ለቀቀችና ወደኔ አቀናች። እርሱም የሞት ሞቱን ዘለለና ሳትቀድመው መሀል መንገድ ላይ
ደረሰባት። የያዘውን መጥረቢያ ሲሰነዝር አንገቷን አገኘው። ዝልፍልፍ ብላ ወደቀች። መንፈራገጥ
ማጉዋራት ጀመረች። ከዚያ ባንድ እጁ እፍስ አድርጎ ደረቱ ላይ ጥብቅ አድርጎ አቀፈኝና
ያባብለኝ፤ እንባዬን እየጠራረገ ይስመኝ፤ ይደባብሰኝ ገባ። አውሬዋ ጥቂት በጣእር ከተንፈራገጠች
በሗላ ዝልፍልፍ ዝም አለች። እኔም ጥቂት ቆይቼ የተረጋጋሁ ብመስልም ሰውነቴ መንቀጥቀጡን
ቶሎ አላቆመም ነበር። አባቴ ከእግሩ ላይ የሚንፏፏውን ደም በእራፊ እየጠራረገና ህመሙን
 
Page 4 of 9 
 
 

ሊውጥ እየታገለ የሞተችውን አውሬ በመጥረቢያው አገላበጣትና “ ቀበሮ ናት ቀበሮ..የታባቷንስ


ይች ሰላቢ…” እኔ ቀበሮን በስሟ እንጂ ከዚያ በፊት በአካል አይቻትም አላውቅ። “የታባቷንስ ይች
ገደቢስ ሰላቢ…” እያለና የሚሰማውን ህመም ሊውጥ እየታገለ ከእግሩ ላይ እየወረደ ያለውን ደም
ለማቆም ጨርቅ ይጠመጥም ገባ። ወዲያውም ድካምና ዝለት ሲሰማው እኔን ከጎኑ አስቀምጦ
ከአንድ ወይራ ዛፍ ስር ግንዱን ደገፍ አለ። የኔ ሰውነቴ በድንጋጤ መንቀጥቀጡን አላቆመም።

ቁስሉን ያሰረበትን ጨርቅ ቢያጠብቀው ቢያላላው ከእግሩ ላይ የሚወርደው ደም ሊቆም


አልቻለም። ድካም እየተሰማው መጣ። ጸሀይ ወደመጥለቂያዋ አሽቆለቆለች። ጥላ ረዛዘመ። የግዱን
ተነሳና እጄን ይዞ ወደ አብየ ከልካይ ቤት አቀናን። ሰላሳ ደቂቃ ያላነሰ ያስኬዳል። አያዘገምን
እቤት ደረስን። አጎቱና ባለቤታቸው ባባቴ ላይ የደረሰውን ሲመለከቱ ደንግጠውና አዝነው የቤቱ
ልጆች ውሀ አሙቀው በጨው አድርገው ቁስሉን አጥበው ደሙን እንዲያቆሙለት መከሩ። የምጣድ
ማሰሻ ቁራጭ ጨርቅ ፍም እሳት ላይ ሞቅ ተደረገና ቁስሉ ተሸፍኖበ፤ ከላይ በንጹህ ጨርቅ
ታሰረለት። ወዲያው ይፈስ የነበረው ደም ቆመ። ይሁንና አባቴ ያተኩሰው ገባ። ብርድ ብርድ
አለኝ ይል ጀመር። እሳትም ነደደለት። ልብስም ተደረበለት። ግና ሌሊቱን ሲያተኩሰው ሲያቃስት
አደረ።

የጀመረውን ምንጠራ ሊቀጥል አልቻለም። በማግስቱ አብየ ከልካይ በቅሎ አስጭነው ሰው


አስከትለው እኔ ከአባቴ ሗላ ተፈናጥጬ ወደ ቤታችን መንገድ ቀጠልን። ከሰዓት በሗላ ደረስን።
እናታችን ወንድሞቼ እና እህቶቼ ሁሉ ተደናግጠው መላቀስ ሲጀምሩ አባቴ ከህመሙ ጋር አየታገለ
የደረሰውን አቅሎ ሊነግራቸው ሞከረ። እናቴ ግን አባቴ እንደዚያ ተዳክሞ አይታው ስለማታውቅ
ለቅሶዋን ማቆም አልቻለችም። እኛም ተከትለናት መንጫጫት ቀጠልን።

ድንጋጤአችንና ለቅሶአችን ያባቴን መንፈስ አወከው። እንደምንም ራሱን ለማጠንከር እየሞከረ


“አትጠገብ ለጊዜው የንፊፊቴ ህመም ሰለበረታ ነው እንጂ ምንም አልሆንኩ። እባክሽ አንቺም
ተደናግጠሽ ልጆቼንም አታስደንግጪአቸው። በቃሽ የኔ ዓለም። በቃችሁ ልጆቼ…” እያለ በደከመ
ድምጽ ሲያበረታታን፤ እናታችን ሰከን ስትል አኛም እሷን ተከትለን ለቅሶአችንን ለመዋጥ
እየሞከርን ገሚስ እግሩን ገሚስ አንገቱን አቅፈን በዙሪያው ተቀመጥን። እሱም ሲያቃስት፤ እኛም
ስናለቅስ፤ መሸ፤ ነጋ።

አንድም ቀን አለፈ፤ ሁለትም፤ ሶስትም፤ አራትም። አባቴ እየባሰበት አንጂ እየተሻለው ሊሄድ
አልቻለም። እናቴ በየገጠሩ መድሀኒት አዋቂዎች ዘንድ ስትሮጥ ከርማ ነበር። ያልታዘዘለት
ስራስርና ቅጠላቅጠል አልነበረም። ሁሉንም እየጨቀጨቀች አጠጥታው ነበር። “ጥቁር ዶሮ
በጭንቅላቱ አዙራችሁ ማታ ልቀቋት” ተብሎ ነበር። ሁሉም ተደረገ። ሁሉም አልሰራም።

ቀናት ቀናትን እየተኩ ነጎዱ። በቤታችን የሀዘን ድባብ ካጠላ ሁለተኛው ሳምንት ተገባደደ።
በልጅነት አእምሮዬ ልሸከመው የማልችለው ጭንቅ እየመጣ ነው። አባቴ ከ እለት እለት እየደከመ
ከመኝታው መንቀሳቀስ ተስኖታል። መጸዳዳቱም በእናቴ ድጋፍ ሆኗል። ሌሊትና ቀን በቤታችን
የማያቋርጥ እንባ ይፈሳል። አባቴ ያቃትታል። ያቃስታል። በቤታችን ተስፋ ጨለመ። እናቴ
ሌሊትም ቀንም በማልቀሷ አይኗ ነፈረ።

ቢቸግራት አንዲት ባለውቃቢ ወይዘሮ ዘንድ መፍትሄ ፍለጋ ሔዳ ነበር። ጭንቀቷን ያዋየቻቸው
ወይዘሮም “ቀይ አውራ ዶሮ አርደሽ፤ በደሙ ሰውነቱን አሻሺውና ከቤት አርቀሽ ሰው
በሚመላለስበት ቀጭን መንገድ ላይ፤ ቂጣ ቆሎ ጨምረሽ፤ ወፍ ሳይንጫጫ፤ ጭለማው ሳይፈታ፤
 
Page 5 of 9 
 
 

ወስደሽ ጣይው። መጀመሪያ የረገጠው አውሬም ሆነ ሰው ጦሱን፤ ልክፍቱን ይዞለት ይሄዳል።


ወዲያው ይነሳና የልጆችሽ አባት ወደእርሻው ይሰማራል።” ብለው መከሯት። እናቴም
የተመከረችውን ሁሉ አደረገች። ግና ያባቴ ህመሙ ይብሱን ጠና እንጂ የተሻለው ነገር
አልነበረም። ሁለተኛው ሳምንት አለፈ።

ያባቴ ሁኔታ ይብሱን አስደንጋጭ እየሆነ ሲመጣ የሰፈሩ ሰው ምን ማድረግ እንዳለበት ተሰብስቦ
መከረ። ቢሞትም ቢድንም ሀኪም ዘንድ ደርሶ እንደሆነ ይሁን ተባለ። ሰፈርተኛው በሙሉ እኛ
ቤት ተሰበሰበና ያለውን ነገር ሊያዋጣ መከረ። አዋጣም። ለጊዜው በጁ ላይ ምንም ገንዘብ
ያልነበረውም ዶሮ ያለው ዶሮውን፤ ፍየል ያለውም ፍየሉን ሸጦ ሊያመጣ ተስማማ። ገሚስ አባቴ
የጀመረውን ምንጣሮ ሊጨርስና የዘር ሰአት ሳያልፍ ያለንን እርሻ አርሶ ሊዘራልን ተስማምቶ ሰው
መረጠ። በሶስተኛው ቀን ሁሉም የገባውን ቃል ሳያጥፍ ያገኘውን ገንዘብ ይዞ መጣ። ወዲያውም
አብሮት ሀኪም ዘንድ የሚቆይ ተብሎ አንድሰው ተመረጠ። እናቴን “አንቺ ልጆቹን ይዘሽ እቤት
ቆይ” ብለው መከሯት።

አንድ ቀን ጠዋት ማለዳ አባቴን በወሳንሳ ተሸክመው የሰፈሩ አርሶ አደሮች ይዘውት ከቤት ወጡ።
ሰላሳ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ወደምትገኝ ከተማ ሊወስዱት ነበር።

የበልግ ዝናብ መጣል ጀምሮ ነበር። አባቴ ህልሙም ቅዠቱም ሁሉ ስለ አዲሱ መሬት ሆኖ ነበር።
ከልክ በላይ ይቃዣል። “የተገመሰውን ማሳ አልዘራሁትም እኮ” ይላል። “የበልግ ዝናብ
እንዳያልፍብኝ ነገ በጠዋት ተነስቼ ዘር እበትናለሁ፡ አትጠገብ በጧት በጧት አስነሸኝ። ባይሆን
ስነሳ አርመዋለሁ። እኮተኩተዋለሁ። እባክሽ ጎረቤት እንዲዘራልኝ አድርጊ….አትጠገብ..አትጠገብ..

አባቴ ይህን ሁሉ ቅዠት በሁለት ሳምንት ልክፍት ሲቃዥ ከእለት እለት እየደከመ ከመኝታው
መነሳት አቅቶት ነበር። የሚያተኩሰው ትኩሳት ውሀ ያፈላ ነበር። እራሴ ተፈለጠ ይል ነበር።
ይበረግግ ነበር። ውሀ ሲፈስ ኡኡ ይል ነበር። ሁለመናዬን አመመኝ ይል ነበር። አፉ ያልታወቀ
ልክፍት።

አሁን ቤታችን በጭንቅና በሀዘን ተውጧል። አባታችንን ሰዎች ተሰብስበው በወሳንሳ ይዘውት
ወተዋል። አንድቀን ካደርን በሗላ እናታችን ለብቻዋ ማንሾካሾክ ማውራት ጀምራለች። የምትለውን
ነገር ሁሉ እሰማታለሁ።

“አዬ…አካሌዋ.. አትሙት.. ልጆቻችንን መች አሳደግንና…ቡቃዮቻችን እኮ ገና ለጋዎች ናቸው።…


ብቻዬንማ አልችለውም አካሌ… አብረንም እየለፋን ያለውን መከራ እያየህ? ተው አካሌ… ተው…”

አይኖቿን አፍጣና መሬት ላይ ተክላ ለረጂም ደቂቃዎች የሚያስጨንቅ ዝምታ ዝምምም ትላለች።
ድንገት ደሞ ሳናስበው ፍንድት ብላ ስቅስቅ እያለች ታለቅሳለች። እኛም ተከትለናት መንጫጫት
እንጀምራለን። ደረቷ ላይ ተለጥፎ እየጠባ ያለው ትንሹ ወንድማችንም መጥባቱን ይተውና በለቅሶ
ከኛ ይቀላቀላል። ከልክ በላይ ስንንጫጫባት የራሷን ለቅሶ ለመዋጥ እየተናነቀች ዝም እንድንል
ታባብለናለች። አንዳንዴም አንሰማሽ ስንላት ቆጣ ትላለች። እኛ ዝም ስንል ትንሹ ወንድማችን
ግን አያቆምም ነበር። እንደገና ደሞ እሱን ተከትለን አናለቅሳለን። በቤታችን ተስፋ ጨለመ።
እናቴ ሌሊትም ቀንም በለቅሶ አይኗ ነፈረ።

 
Page 6 of 9 
 
 

አባቴ ለህክምና ከተወሰደ አንድ ሳምንት አለፈ። ምንም ወሬ ከከተማ አልመጣም። አብየ ከልካይ
ያባቴን ሁኔታ ሊያረጋግጡ ከደጋ መተው ነበር። ያለበትን ቦታና ሁኔታ ስንነግራቸው
የበቅሎአቸውንም ኮርቻ ሳያወርዱ “ያለበትን ሁኔታማ ማየት አለብኝ ብለው” ቡና እስኪፈላላቸው
እንኳን አልጠበቁም ወደከተማ አቀኑ። እሳቸውም በዚያው እልም ብለው ቀሩ። ወሬውን እንኳን
ይዞልን የሚመለስ ሰው ጠፋ።

ቀናት ቀናትን ተኩ። ሳምንታት ተከታተሉ። ያባቴ ነገር የውሀ ሽታ ሆኖ ቀረ። እናታችን ነፍስና
ስጋዋ ሲሟገቱ ነው የከረመችው። ቤታችን ጨልሞ ነው የከረመው። አንድ ወር ተቆጠረ።አይደርስ
የለ የጭንቀታችን የመጨረሻው ቀን ደረሰ።

አንድ እሁድ ጠዋት ብዙ ሰዎች ወደኛ ቤት የሚመጡ ይመስላል። በር ላይ ቆመን እናታችን


አንጋጣ እያየች ነበር። እንደ አልጋ አይነት ነገር የተሸከሙ መንደርተኞች አንድ የተከናነበ ሰው
የተጫነች በቅሎ አጅበው፤ ገሚስም በህብረት የተሸከሙትን ነገር ለመተጋገዝ እየተቀባበሉ
ይመስላል በርጋታ ወደኛ ቤት እየቀረቡ እየቀረቡ መጡ። እናታችንን ከመሀል አድርገን ዙሪያ
ቀሚሷን ጨምድደን ይዘን፤ በድንጋጤ ወደቤታችን የሚያዘግሙትን ሰዎች መመልከት ቀጠልን።
ሰዎቹ ከባድ የሚመስለውን ነገር ተሸክመው እየተንገዳገዱ ከበቅሎዋ ፊትፊት አንዳንዴም ወደሗላ
ቀረት እያሉ ወደቤታችን ቀረብ አሉ። እናታችን ድንገት መሬት ላይ ተፈጠፈጠች። ደረቷን
እየደበደበች መጮህ ጀመረች። ድንገት መርዶ የተነገረው ሰው ይመስል “ ወየው አካሌን…ወየው
አካሌን ኡ..ኡ…” እኛም ተከትለናት ምድሩን ቀውጢ አደረግነው። አዎ። የፈራችውም ነገር ደረሰ
ብላ ነው መሰለኝ፤ አፈር እያፈሰች በላይዋ ላይ ትበትን፣ ትበትን፤ ትበትን፤ ትጮህ ጀመር።

ወደቤታችን ከተጠጉት መንደርተኞች አንዱ ጉረቤታችን ድንገት በሚያስደንቅ ፍጥነት


ከመሀከላቸው እየተንደረደረ በር ላይ ደረሰና እናቴን ከወደቀችበት አንድትነሳ እጆቹን
እያንቀጠቀጠ፤ ሲለምናት “ወይዘሮ አትጠገብ …ወ..ወ..ወይዘሮ አትጠገብ …ለ..ለ ለምን
አልሞተም ማለትሽ ነው የልጆችሽ አባት? አረ ባዛኝቱ… ድኗል እኮ… ድ..ድኗል…ዝም በሉ.. ዝም
በሉ ልጆች አባታችሁ ድኗል”

ባለማመን አይኖቻችንን ስንገልጥ አባታችን በቅሬታ ፈገግ እያለ ቀስ ብሎ ከበቅሎ ሲወርድና


እጆቹን ዘርግቶ ወደኛ ሲመጣ አየነው። ፍጹም በደከመ ንግግር “አ.ት..ጠ. ገብ ዳንኩ እኮ፤ ዳ..
ንኩ… ልጆቼ ተሻለኝ እኮ…” እያለ ሲስመን እናቴ ማመን አልቻለችም ነበር። እንባዋን
እየጠረገችና ለቅሶዋን ለመዋጥ እየታገለች መሬቷን አስርአስሬ ትስም ገባች። መንደርተኞቻችን
በወሳንሳ የተሸከሙትን ነገር ቀስ ብለው አወረዱና ወደ ቤት ሲያስገቡት አንድ ኩንታል ጤፍ
ሸምተውልን እንደመጡ ለናቴ ነገሯት።አረጋግተውን አባታችንን በህይወት አስረክበውን
ወደየቤታቸው ተበተኑ። አብየ ከልካይም እየተጣደፉ በቅሎአቸውን ጭነው ወደቤታቸው አቀኑ።

አባቴ ደከም ብሎታል እንጂ ህይወት ከገጽታው ትነበባለች። ህያው ፈገግታ ከፊቱ ይበራል።
የእብድ ውሻ በሽታ እንደለከፈው ሀኪም መናገሩን ነገረን። የተሰጠው መድሀኒት ቁና ሙሉ ነበር።
ያንን እየዋጠ ሶስት ሳምንታት አለፉ። ብርታትና ህይወት በቤታችን ተመልሰዋል። ወር አለፈ።
አባቴ መድሀኒቱን ጨርሷል። ዳነ። በቤታችን ብርሀን በራ።

የማሳችን ቡቃያ በቅሎ አምሮበታል። ያየው ሁሉ ይናገራል። የአረምና የኩትኳቶ ጊዜ ደርሷል።


አባቴ ሊያርምና ሊኮተኩት ወደ ደጋ ሊወጣ በመሰናዳት ላይ ነበር።

 
Page 7 of 9 
 
 

አንድቀን ጠዋት እደጅ ጨወታ ላይ ነበርን። አባቴ መኮትኮቻ ትከሻው ላይ አድርጎ፤ እናቴ
አገልግል ይዛ ልትሸኘው ከቤት እየወጣ ሳለ ሁላችንንም ከሳመን በሗላ እኔን በፈገግታ
እየተመለከት እንዲህ አለ፤

“ወደ አዲሱ እርሻችን መሄዴ ነው፤ በድሉ አብረኸኝ ትሄዳለህ?” ሳቅ እያለ ጠየቀኝ።

‘’ አ..አአ… ቀበሮ ትበላኛለች ” አልኩት ። ይብሱን ሳቀ።

የዚያን እለቱ ሁኔታ ባይምሮዬ ይመላለስ ጀመር። አባቴ ከቤት ወቶ በቅጠላቅጠሉ ውስጥ ቁልቁል
የምትወርደውን ቀጭን መንገድ ሲይዝ ያለፈውን እያሰብኩ ባይኔ ስከተለው ዶማና መኮትኮቻውን
በጀርባው በኩል ትከሻው ላይ እንደጫነ ከአይኔ ተሰወረ። ያቺ አውሬ እንደ ግዙፍ ተራራ ጎልታ
አይኔን ጋረደችው። ወደ ጨዋታዬም ተመለስኩ። አባቴም ነጎደ።

ልመናዬ

ዛሬ የኢትዮጵያ ህዝብ በትልቅ እስር ቤት ውስጥ የሚኖር ምርኮኛ ነው።ታንክና መድፍ ከቦት
ነው በመኖር ላይ ያለው።ዙሪያውን በጆሮጠቢ ታጥሮ ነው በመኖር ላይ ያለው።ከውጭ የሚመጣ
ዜና አይሰማም። ኢንተርኔት የለውም።በሀገር ውስጥ የነጻው ፕሬስ ጋዜጦች በሙ ሉ ተዘግተው
ጋዜጠኞቹም ሁሉ ስለተሰደዱ በሀገሪቱ ውስጥ እየተካሄደ ያለውን እውነተኛ ነገር የሚያውቅበት
እድል የለውም።ዙሪያውን ሀያ አራት ሰአት እየጮ ሁ የሚያደነቁሩት በውሸት የተሞሉት የወያኔ
ቴሌቪዥንና ሬዲዮ እና ጋዜጣው ናቸው ።

የኢትዮጵያን ህዝብ ከኢንፎርሜሽን አፈና ለማውጣት፤ሕዝቡ ምን እየተሴረበት እንዳለ፤በየክፍለ


ሀገሩ ምን ወንጀል እየተፈጸመበት እንዳለ፡ረሀቡን፤የተፈጥሮ አደጋውን፤የመብት ረገጣውን፤ሕገወጥ
ግድያውን፤ ዘረፋውን ፤የኑሮ ውድነቱ ያለበትን ደረጃ፤ከወያኔ መገናኛ ብዙሀን ሊያገኝ
ስለማይችል ለህዝቡ የቆመ የዜና ምንጭ ያስፈልጋል።እስከ ምርጫ 97 ያንን ቅዱስ የጀግና
ተግባር ነጻው ፕሬስ ሲወጣ ነበር።አሁን ግን ነጻ ፕሬስ በኢትዮጵያ የለም።አንድ ብቸኛ መፍትሔ
ግን ባለፈው አንድ አመት ብቅ ብሏል።የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቪዥን።ይህንንም ቴሌቪዥን
ወያኔ ከቻይና መንግስት ጋር እየተመሳጠረ በየጊዜው ያፍነዋል።ይህንን ጣቢያ በገንዘብ ማጠናከር
ያለብን እኛው ነን።ወያኔና ሻእቢያ ሀገራችንን ለመጣል ሲታገሉ ደጋፊዎቻቸው ሁሉ እንዴት
ይተባበሩ እንደነበር መዘንጋት የለብንም።እኛ ነጻ ለመውጣት መተባበር የለብንም ? የህይወት
መስዋእትነት አይደለም የሚጠይቀው፤ትንሽ ገንዘብ እንጂ።የኢትዮጵያ ህዝብ የለት ተለት ችግሩና
መከራውን መሬት ላይ ያለውን እውነት መስማት ማየት አለበት።የወያኔ ውሸት ሰለባ ከመሆን
እናድነው።በዚህ ጽሁፍ አቅራቢ ግምት ከስድስት ሚሊዮን የማያንስ ኢትዮጵያዊ ባለም ላይ
ተበትኖ ይገኛል።ቢያንስ ቢያንስ አንድ ሚሊዮን ሀገሩን የሚወድ ኢትዮጵያዊ ይጠፋ ይሆን ?
ይህ አንድ ሚሊዮን ሰው በየወሩ ሀያ ብር ብቻ ቢያዋጣ የወያኔን አፈና ተቋቁሞ ሀያ አራት ሰዓት
ለኢትዮጵያ ህዝብ እውነትን የሚያስተላልፍ ቴሌቭዢን ይኖራል።ሀያ ብር ማለት ደግሞ አንድ
ቅዳሜ መሸታ ቤት ጎራ ብለን ከምናቀልጠው ገንዘብ ጋር ሲነጻጸር ምንም ማለት
አይደለም።እባካችሁ እባካችሁ ይህን ጽሁፍ አንብባችሁ እንደጨ ረሳችሁ www.ESAT.com
የሚለውን በማውስ ጠቁሙ ና አንድ ነገር አድርጉ።እንደ አኬልዳማ አይነቶቹን የወያኔ ውሸቶች ፤
እውነቱን በማቅረብ ነው ህዝቡን መታደግ የሚቻለው ። ጸሀፍትም ሁሉ በየጽሁፎቻችሁ መጨ ረሻ
ላይ ይህንን ልመና አቅርቡ ።

ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር

lkebede10@gmail.com

 
Page 8 of 9 
 
 

 
Page 9 of 9 
 

You might also like